የሐዘን መግለጫ
በካናዳ የኢትዮጵያውያን ስፖርት እና ባህል ፌዴሬሽን በቀድሞው የኢትዮጵያ ብሔራዊ እግር ኳስ ቡድን ተጫዋች ፍስሃ ወልደአማኑኤል ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን ይገልጻል።
ፍስሃ ወልደአማኑኤል በኢትዮጵያ እግር ኳስ አንጸባራቂ ታሪክ ከፃፉ ድንቅ ሰዎች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀሱና በእግር ኳሱ ታሪክ ውስጥ ቁጥር አንድ ላይ የሚቀመጡ ናቸው። በሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ድል ልባቸው ወደ እግር ኳሱ የተሳበው ፍስሀ ወልደአማኑኤል ከአራተኛው እስከ ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ድረስ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተሰልፈው መጫወታቸው ይታወሳል።
መገኛቸው ሐረር የሆነውና ከዛው የተነሳው የእግር ኳስ ህይወታቸው እስከ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ድረስ ትልቅ ስኬትን ፈጥሮላቸዋል።
በቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ በተጫዋችነትም ድንቅ ሚና ማሳለፍ የቻሉ ሰው እንደነበረ ታሪካቸው ያሳያል። ከቅዱስ ጊዮርጊስ በኋላ ወደ አሜሪካ በመሄድም ከተዋቂዎቹ ቦቢ ቻርልተንና ጆርጅ ቤስት ጋር እግር ኳስ የመጫወት እድልን አግኝተዋል።
በቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ የቡድን መሪ በመሆንም ግልጋሎት ሰጥተዋል። በጠንካራ ሹታቸው ይታወቁ የነበሩት ፍስሀ ለእግር ኳስ ባላቸው ፍቅር ኳስ ፊደሉ የሚል መጠሪያንም አግኝተዋል።
በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያን ስፖርት ፌዴሬሽን (ESFNA) በአመራርነትና በተለያዩ ኃላፊነቶች ያገለገሉ ሲሆን፣ በቅርቡም የዕድሜ ልክ የህይወት ዘመን ግልጋሎት ማስታወሻ የካባ ሽልማት ከፌዴሬሽኑ ተበርክቶላቸው እንደነበር ይታወቃል፡፡
በካናዳ የኢትዮጵያውያን ስፖርት እና ባህል ፌዴሬሽን በዚህ ታላቅ እግር ኳሰኛ ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን እየገለጸ፤ ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸውና ለእግር ኳስ አድናቂዎቻቸው በሙሉ መጽናናትን ይመኛል!



